ምሥጢረ ቁርባን

ምሥጢረ ቁርባን

ቁርባን ፤ ማለት ፣ ለእግዚአብሔር የሚቀርብ አምኃ ፣ መስዋዕት ፣ መንፈሳዊ ነገር ሁሉ ማለት ሲሆን ፤ በዚህ ትምሕርታችን ግን ፤ ስለ ሐዲስ ኪዳን መስዋዕት (የክርስቶስ ሥጋና ደም) እንማራለን ።

በብሉይ ኪዳን ለሐዲስ ኪዳን ቁርባን (መስዋዕት) ምሳሌዎች

  • የመልከ ጼዴቅ መስዋዕት ዘፍ 14 ፥ 18 ። ዕብ 5 ፥ 6 ። ዕብ 6 ፥ 1 ። ህብስቱ የሥጋው ፤ ወይኑ የደሙ ምሳሌ ፤ መልከ ጼዴቅ የክርስቶስ ፤ አብርሐም የምዕመናን ።
  • የእስራኤል ፋሲካ ። ዘፀ 12 ፥ 1 ። ሞት የዲያብሎስ ፤ እስራኤል የምዕመናን ፤ በጉ የክርስቶስ ምሳሌ ።
  • የእስራኤል መና ። ዘፀ 16 ፥ 13 ። መና የጌታችን ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደም ፤ እስራኤል የምዕመናን ፤ ደመና የእመቤታችን

በብሉይ ኪዳን መስዋዕት ቁርባን ያቀረቡና በረከት ያገኙ አባቶች

  • አዳም አባታችን አዳም ባቀረበው መስዋዕት ከአምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን በኋላ ሰው ሆኖ እንደሚያድነው ቃል ገባለት ። ዘፍ 3 ፥ 22 ። ገላ 4 ፥ 4 ።
  • ኖኅ ባቀረበው መስዋዕት ለኖኅና ለልጆቹ ምድርን ዳግም በመቅሰፍት እንደማያጠፋት በቀስተ ደመና ምልክት ቃል ገባላቸው ። ዘፍ 9 ፥ 1 ። ዘፍ 9 ፥ 8 ።
  • አብርሐም ዘፍ 18 ፥ 3 ። አባታችን አብርሐም ባቀረበው መስዋዕት በዘርህ አሕዛብ ሁሉ ይባረካሉ የሚለውን የተስፋ ቃል ሰማ ፤ ያም ዘር የተባለው ለጊዜው ይስሐቅ ሲሆን፤ ፍጻሜው ግን ለጌታ ነበር ።
  • መልከ ጼዴቅ ዘፍ 14 ፥ 17 ። መዝ 109 ፥ 4 ። ዕብ 5 ፥ 6 ። በእግዚአብሔር ፊት ባቀረበው መስዋዕት ክህነቱ ለዘለዓለም ተብሎለት የክርስቶስ ምሳሌ ሆነ ። ዕብ 7 ፥ 1 ።
  • ዳዊት መዝ 131 ፥ 11 ። መስዋዕት ባቀረበበት ሠዓት ከአብራክህ የተገኘው ልጅህ በዙፋንህ ይነግሣል ተባለለት ፤ ይህም ለጊዜው የተነገረው ለሰሎሞን ሲሆን ፍጻሜው ለክርስቶስ ነበር ። መዝ 71 ፡1 ። ሌሎችም በእግዚአብሔር ፊት ንጹህ መስዋዕታ ቸውን እያቀረቡ በረከት ተቀብለዋል።

ምሥጢረ ቁርባን በሐዲስ ኪዳን

በብሉይ ኪዳን ዘመን ይቀርብ የነበረው የመስዋዕት ቁርባን ፤ ከበግ ፤ ከላምና ፤ ከተለያዩ እንስሳት ነበር ። በሐዲስ ኪዳን ግን እንስሳት በቤተ መቅደስ ውስጥ መስዋዕት (ቁርባን) ሆነው አይቀርቦም መስዋዕት ሁሉ በክስቶስ ሥጋና ደም ተጠቃሏል ።
ይህንም የአዲስ ኪዳን መስዋዕት የመሠረተው ራሱ ጌታችን ሲሆን ፤ በጸሎተ ሐሙስ ማታ አስራ ሁለቱ ሐዋርያት እንዳሉ በመጀመሪያ መስዋዕተ ኦሪትን ሰርቶ ካሳለፈ በኋላ ኅብስቱና ወይኑን ባርኮ “ነገ በመስቀል ላይ የሚቆረሰው ሥጋዬና የሚፈሰው ደሜ ይህ ነው ብሉ ጠጡ ብሎ ሰጣቸው” ። ማቴ 26 ፥ 26 ።

ዛሬ ካህኑ ኅብስቱን በጻህል ወይኑን በጽዋ አድርጎ ጸሎተ ቅዳሴውን እየጸለየ.. ሲባርከው እንደዚያ ጊዜው ኅብስቱ ተለውጦ ሥጋ መለኮት ወይኑም ተለውጦ ደመ መለኮት ይሆናል ። ይህንም ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደም በምንቀበልበት ጊዜ ለእኛ ሲል የተቀበለውን መከራና ስቃይ እያሰብን ራሳችንን በንስሓ ከኃጢአት ንጹህ አድርገን ከንስሓ የቀረውን በደላችንን እንደሚደመስ ስልን ፤ ከበደል እንደሚያነጻንና የዘለዓለም ሕይወት እንደሚሰጠን አምነን መሆን አለበት ።

በ1ቆሮ 11 ፥ 23 “ይህንም ለመታሰቢያዬ አድርጉት ” የሚለው ቃል ሥጋውንና ደሙን በምንቀበልበት ጊዜ ስለሰው ልጆች ሲል በቀራንዮ አደባባይ የተበውን መከራና በልባችን ውስጥ የተሳለውን አምላካዊ ፍቅሩን እያስታወስን እንድንኖር ነው መታሰቢያ የሚለው ቃል የሚያመለክተው የማይረሳ ነገርን ነውና ። ገላ 3፥1

ጌታችን ይህን ምሥጢር ከማሳየቱ (ከመመስረቱ) በፊት በዮሐ 6 ፥ 25-8 ። “ሥጋዬን ካልበላችሁ ደሜንም ካልጠጣችሁ በራሳችሁ ሕይወት የላችሁም ሥጋዬን የበላ ደሜንም የጠጣ የዘለዓለም ሕይወት አለው ። ሥጋዬ እውነተኛ መብል ደሜም እውነተኛ መጠጥ (ሕይወትን የሚሰጥ) ነው ” በማለት ስለምሥጢረ ቁርባን በስፋት አስተምሯል ።

የቅዱስ ቁርባን ጥቅም

  • ከዚህ ዓለም በሞት ብንለይም እንኳን በሰማያዊ መንግስት የማያልፈውን የዘለዓለም ሕይወት እናገኛለን ። ዮሐ 6 ፥ 54 ።
  • ለኃጢአታችን ስርየት (ፍጹም ድኅነት) እናገኛለን ። ማቴ 26 ፥ 26 ።
  • ከጌታችን ጋር ከቅዱሳንም ጋር ያለንን አንድነት እናረጋግጠጣለን ። 1 ቆሮ 10 ፥ 17 ።

ሥጋውን በስንዴ ደሙን በወይን ያደረገበት ምክንያት ትንቢቱንና ምሳሌውን ለመፈጸም ነው

ትንቢት
በልቤ ደስታ ጨመርሁ ከስንዴ ፍሬና ከወይን ፍሬ በዛ ። መዝ 4 ፥ 7 ። ይህም ቃል እውነተኛና ፍጹም የሆነው ዘለዓለማዊ መድኃኒት ቅዱስ ቁርባን በስንዴና በወይን እንደሚደረግ ያመለክታል ።

ምሳሌ
የክርስቶስ ምሳሌ፤ መልከ ጼዴቅ መስዋዕት የሚያቀርበው በስንዴና በወይን ስለነበረ ምሳሌውን ለመፈጸም ። ዘፍ 14 ፥ 17 ።

ሥጋውንና ደሙን በምግብ ያደረገበት ምክንያት

  • ምግብ ከሰውነት ጋር እንደሚዋሃድ ሥጋውንና ደሙን ስንቀበል በእውነት እንደሚዋሃደን ለማስረዳት።
  • ምግብ ለሥጋችን ኃይል እንደሚሆነን ሥጋውና ደሙም ለነፍሳችን መንፈሳዊ ኃይል ይሰጠናል።
  • አዳምና ሄዋን በምግብ የእግዚአብሔር ልጅነታቸውን እንዳስወሰዱ ፤ በቅዱስ ሥጋውና በክቡር ደሙ ልጅነታችንን ሊመልስልን ። ዘፍ 3 ፥ 1 ። ዮሐ 6 ፥ 49።
  • ቅዱስ ቁርባንን ፤ በበላችን ንስሓ ከገባን በኋላ ሁልጊዜ መቀበል ይገባናል ። የኃጢአታችን ስርየት የሚረጋገጠው በቅዱስ ቁርባን ነውና ። ማቴ 27 ፥ 27።

ምዕመናን በሕይወት እስካሉ ደረስ ወንድም ይሁን ሴት ፣ ታናሽም ይሁን ታላቅ ከቅዱስ ቁርባን መለየት የለባቸውም ይህ ምሥጢር በፆታ በዕድሜ የማይገደብ ለሁሉ የተሰጠ ነውና ። ዮሐ 6 ፥ 54 ። በሰራነው ስህተት ተጸጽተን ንስሓ ሳንገባ በድፍረት ሥጋውንና ደሙን መቀበል የለብንም ፤ ይህን የሚያደርጉ ሰዎች ዕዳ አለባቸው ። 1ቆሮ 11 ፥ 27 ። የምንቀበለው ቅዱስ ቁርባን ጌታችን በቀራንዮ አደባባይ ተሰቅሎ ከዋለ በኋላ ፤ ዘጠኝ ሰዓት ሲሆን በራሱ ሥልጣን ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው ለይቷል ። ዮሐ 10 ፥ 18 ። ዮሐ 19 ፥ 30 ። በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ሄዶ በዚያ የነበሩ ነፍሳትን ወደ ገነት ከመለሰ በኋላ ሶስት መዓልትና ሶስት ሌሊት በከርሠ መቃብር ከነበረው ሥጋ ጋር በፈቃዱ አዋህዶ ተነሳ ፤ በዚህ ጊዜ ውስጥ ግን(ሥጋውና ደሙ በተለያዩበት ወቅት) መለኮት ፣ ከነፍ ስም ከሥጋም ጋር አልተለየም ። 1ዼጥ ። ስለዚህ እኛ የምንቀበለው ሥጋና ደም ፤ ነፍስ የተለየችው መለኮት የተዋሃደው ነው ። 1ዼጥ 3 ፥ 18 ።