ምሥጢረ ሥጋዌ

ምሥጢረ ሥጋዌ

ሥጋዌ : ተሰገወ ሰው ሆነ ካለው የግዕዝ ቃል የተገኘ ሲሆን : ምሥጢረ ሥጋዌ ማለት ሰው የመሆን ምሥጢር ማለት ነው::

አምላክ ለምን ሰው ሆነ?

1. አዳምን ከበደል ሊያነጻው
አዳም የሰይጣንን ምክር በመስማት እግዚብአሔር አትብላ ያለውን ዕፀ በለስ በልቶ ትእዛዙን በማፍረሱ ከፈጣሪው በተጣላ

ጊዜ የሞት ፍርድ (ሞተ ሥጋ ሞተ ነፍስ) ተፈረደበት ። ዘፍ 3፥1 ። ለጥፋቱ ምክንያት የነበሩት ዕባብና ሄዋንም እንደ ጥፋታቸው መጠን ተረግመዋል ። ዘፍ 3፥14 ።

አዳምም ጥፋቱን አምኖ ንስሓ ስለገባ አምላክ ሰው ሆኖ እንደሚያድነው ቃል ገባለት ። ዘፍ 3 ፥ 22 ። ቃል ኪዳኑም “አዳም ከእኛ እንደ አንዱ ሆነ” የሚለው ሲሆን እግዚአብሔር ወልድበተለየ ስሙ ፣ በተለየ ግብሩ ፣ በተለየ አካሉ ፣ ሰው ሆኖ እንደሚ ያድነው ቃል መግባቱን ይገልጻል ።

ለአዳም በገባው ቃሉ መሰረት ጊዜው ሲደርስ ከተፈረደበት ፍርድ ነፃ ሊያወጣው (ሊያድነው) ሰው ሆነ ። ገላ 4 ፥ 4 ። ጊዜው ማለት አምስት ሺህ አምስት መቶ (አምስት ቀን ተኩል ሲፈጸም) ማለት ነው ። መዝ 84 ፥ 4 ።

2. የሥጋን በደል ለመካስ
አዳም ፤ ዕፀ በለስን በበላህበት ቀን ሞትን ትሞታለህ (ዘፍ 2፥ 17) ያለውን አምላካዊ ቃል ተላልፎ በለስን በመብላቱ የሞት ፍርድ ከተፈረደበት በኋላ ንስሃ በመግባቱ አምላክ ትሞታለህ ያለው ፍርዱ ሳይሻር ይቅር ይለው ዘንድ ወደደ ። በመሆ ኑም በመለኮታዊ ባህርዩ ሞት ስለማይስማማው የሚሞት ሥጋን ለብሶ (ሰው ሆኖ) ቅጣቱን ሊቀበልለት ። ኢሳ 53፥1 ። የእግዚአብሔር ቸርነቱ የባህርዩ ስለሆነ ሞቱን ሞቶ ፍርዱን በመፈጸም ይቅር ብሎ ቸርነቱን በማድረግ ፍርዱንም ይቅር ባይነቱንም በአንድ ጊዜ ሊገልጽ ፈቃዱ ስለሆነ

3. ፍቅሩን ለመግለጽ
እኛ ሰዎች ምንም ያህል ሰውን ብንወድ ቁሳዊ ነገር ልንሰጥ እንችላን ። እርሱንም ቢሆን ጥቅማችንን (ትርፋችንን)አይተን ነው ። አምላካችን ግን ከእኛ ምንም ላያገኝ ባህርዩን ዝቅ አድርጎ ደካማ ባህርያችችንን በመዋሃድ በአዳም የተፈረደውን ፍርድ እርሱ ተቀብሎ በማዳን እውነተኛ ፍቅሩን ሊገልጽልን ስለወደደ ። ዮሐ 15 ፥ 13 ። ዮሐ 10 ፥ ፲፩ ። ኢሳ 40 ፥ 11 ።

እንዴት ሰው ሆነ ?

1. የሚወለድበት ጊዜው ከመድረሱ አስቀድሞ በነቢያት አድሮ ምሳሌ አመስሏል ትቢት አናግሯል ።
ምሳሌ

  • የመልከ ጼዴቅ ክህነት። መልከ ጼዴቅ የጌታ ፤ አብርሐም የምዕመናን ። ዘፍ 14 ፥ 18 ። ዕብ 7፥ 1 ።
  • የይስሐቅ ቤዛ ሆኖ የተሰዋው በግ። ዘፍ 22 ፥18 ። ይስሐቅ የአዳም ፣ በግ የጌታ ምሳሌ ። ዮሐ 1፥29 ።
  • የእሥራኤል መና ። ዘፀ 16 ፥ 13 ። እሥራኤል የአዳም ፣ መና የጌታ ምሳሌ ። ዮሐ 6 ፥ 32 ። ግብፅ የሲኦል ፤ ከነዓን የመንግስተ ሰማያት ፤ ባህረ ኤርትራ የኃጢአት ፤ የሙሴ በትር የመስቀል ፤ ምሳሌ ሲሆን ሌሎችም በርካታ ምሳሌዎች አሉ።

ትንቢት

  • እግዚአብሔር በሴም ቤት ይደር ። ዘፍ 9፥26 ። እግዚአብሔር የተባለው ወልድ ቤት እመቤታችን ።
  • በዘርህ አሕዛብ ሁሉ ይባረካሉ ። ዘፍ 20፥17 ። ዘር የተባለ ጌታ አሕዛብ የተባሉ ሰዎች ። ገላ 3 ፥16 ።
  • ኮከብ ከያዕቆብ ይወጣል ። ዘኁ 24፥17 ። ኮከብ የጌታ ፤ ያዕቆብ የሰው ልጅ ምሳሌ ። ማቴ 2 ፥ 7 ።

2 ብስራተ መልአክን በተቀበለችበት ሰዓት
መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል እመቤታችንን ባበሰራት ጊዜ እንደ ቃልህ ይደረግልኝ ብላ ስትቀበል ቃሏን ምክንያት አድርጎ መለኮታዊ ባህርዩን ከሰው ደካማ ባህርይ ጋር በማዋሀድና ከሁለት አካል አንድ አካል ፤ ከሁለት ባህርይ አንድ ባህርይ በመሆን ፍፁም ሰው ፤ ፍፁም አምላክ ሆነ ። ይህም ማለት መለኮታዊ ባህርዩን ከሰው ባህርይ ጋር አንድ አድርጎ(አዋህዶ) ሰውና አምላክ (ፍጹም ሰው ፤ ፍጹም አምላክ) ሆነ ። ሉቃ 1 ፥ 30 ። ማቴ 1 ፥ 23 ። ዮሐ 1 ፥ 14 ።

3 ሲዋሃድም

  • እንበለ ውላጤ፤ ያለ መለወጥ።
  • እንደ ሎጥ ሚስት ። ዘፍ 19 ፥ 26 ። እንደ ቃና ውሃ ። ዮሐ ፡ 2 ፥ 1 ። ያይደለ ።
  • እንበለ ቱሳሄ ፤ ያለመቀላቀል።
  • እንደ ማርና ውሃ ሳይቀላቀሉ ፤ በመጠባበቅ ቃልም ሥጋም ባህርያቸው ሳይለወጥ ።
  • እንበለ ቡዓዴ ፤ ያለ መለያየት።
  • እንደ ጥሬ እህል መለያየት ሳይኖር ከሥጋዌ በኋላ በተዋህዶ ይኖራል ።
  • እንበለ ኅድረት ፤ ያለ ማደር።
  • እንደ ልብስና ሳጥን ሳይሆን ፤ እንደ እሳትና እንደ ብረት ባለ ተዋሕዶ ።
  • እንበለ ትድምርት ፤ ያለ መጨመር።  ዕቃ በዕቃ ላይ እንደሚደራረብና ሲፈለግ እንደሚለያይ ሳይሆን ፤ መለኮቱ ከትስብዕቱ (ከተዋሃደው ነፍስና ሥጋ) ጋር በፍፁም ተዋሕዶ አንድ በመሆን ተወለደ ።

ከማን ተወለደ ?

አምላክ የተወለደው ከእመቤታችን ከቅድስተ ቅዱሳን ከንጽህተ ንጹሃን ከድንግል ማርያም ሲሆን ፤ ከሷ እንደሚወለድም ፤ በእግዚአብሔር መነንፈስ በተቃኙ ቅዱሳን አማካኝነት አስቀድሞ ፤ ምሳሌ ተመስሏል ፤ ትንቢት ተነግሯል ።

ምሳሌ

እግዚአብሔር በሴም ድንኳን ይደር ። ዘፍ 9 ፥ 26 ። ድንኳን የእመቤታችን ፤ እግዚአብሔር ሰው የሆነው ጌታ ምሳሌ ።
የአብርሐም ድንኳን ። ዘፍ 10 ፥ 18 ። ድንኳን የእመቤታችን ፤ በአብርሐም ቤት የተስተናገደው እንግዳ የራሱ ጌታ ምሳሌ
የያዕቆብ መሰላል ። ዘፍ 28 ፥12 ። መሰላል የእመቤታችን ፤ በመሰላሉ ላይ የተቀመጠው ንጉሥ የክርስቶስ ምሳሌ ።
የሙሴ ዕፅ ፥ሐመልማልና ነበልባል ። ዘፀ 3 ፥ 2 ። ሐመልማል የእመቤታችን ነበልባል የመለኮት ምሳሌ ። ውዳ ማር ።
የሙሴ ጽላት ። ዘፀ 31 ፥ 18 ። የጽላቱ ማደሪያ የሆነው ታቦት የእመቤታችን ፤ ጽላት የጌታ ምሳሌ ።
የጌዴዎን ፀምርና ጠል ። መሳፍ 6 ፥ 36 ። ፀምር የእመቤታችን ፤ ጠል የጌታ ፤ ምሳሌ ።

ትንቢት

“ሄዋን ትባል ” ። ዘፍ 2 ፥ 22 ። ሄዋን ማለት እመህያዋን ማለት ነው ። ይህ ስም የተሰጠው ለእመቤታችን ነው ። የመጀ መሪያዋ ሄዋን ሞትን ያመጣች ስትሆን ፤ እመቤታችን ግን የሕይወት ባለቤት የሆነው ጌታ ከእሷ ስለተገኘ መሠረተ ሕይወት የሕይወት መገኛ ብለን እንጠራታለን ። መዝ 45 ፥4 ። ልዑል ማደሪያውን ቀደሰ ። ልዑል የተባለው አምላክ ሲሆን ፤ ማደሪያው የተባለች ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በማህፀኗ ተሸክማ የወለደችው የአምላክ እናት እመቤታችን ናት ።

የተቆለፈች ገነት ። መኃ 4 ፥ 45 ። ይህ እመቤታችን አምላክን በድንግልና መውለዷንና ዘለዓለማዊ ድንግልናዋን የሚያስረዳ ሲሆን ፤ በተጨማሪም በህዝቅኤ 44 ፥ 1 ። ላይ ያለው ይህን ግልጽ ያደርገዋል ።

 እነሆ ድንግል ወልድን ትወልዳለች ስሙንም አማኑኤል ይሉታል። ኢሳ 7 ፥ 14 ። ይህ ቃል በቀጥታ የእመቤታችንን የአምላክ እናትነቷን ይገልጻል ። ድንግል የተባለች እሷ ፤ ወልድ (ልጅ) የተባለ ልጇ አማኑኤል ኢየሱስ ክርስቶስ ነውና ።

የነቢያት ትንቢት ሲፈጸም ፤ በህጋዊና በተቀደሰ ጋብቻ ከሚኖሩ ኢያቄምና ሐና በብሥራተ መልአክ እመቤታችን እንድት ወለድ አደረገ የተወለደችውም አዳምና ሄዋን ሳይበድሉ በነበራቸውና መርገም (ጥንተ አብሶ የመጀመሪያ በደል) ባልተላለፈበት ንፁህ አካል ነው ። ከእሷ የሚወለደው አምላክ ለባህርዩ ኃጢአት ስለማይስማማው ፤ የሰዎችን ሁሉ በደል ለመቀበልም ንፁህ መሆን ስላለበት ፤ ይህንም ከአምላክ በቀር የሚያሟላ ባለመኖሩ ፤ ከእሷ ሊወለድ ከመርገም ንፁህ እንድትሆን አደረገ ።

እመቤታችን ነሐሴ 7 ተፀንሳ ግንቦት 1 ሊባኖስ በሚባል ቦታ ተወለደች ። ኢያቄምና ሐና የወለዷት በስለት ስለነበረ በተወለደች ከሶስት ዓመቷ ጀምሮ ለ12 ዓመታት ያህል በቤተ መቅደስ አደገች ። 15 ዓመት ሲሆናት መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ተልኮ መጥቶ አምላክን ትውልጃለሽ ብሎ ባበሰራት ጊዜ እንደ ቃልህ ይደረግልኝ ብላ ስትቀበል ቃሏን ምክንያት አድርጎ አምላክ ከሥጋዋና ከነፍሷ ከፍሎ ከመለኮቱ ጋር በማዋሃድ መጋቢት 29 ተፀንሶ ታህሳስ 29 ተወለደ ። በዚህም ከሁለት አካል አንድ አካል ከሁለት ባህርይ አንድ ባህርይ ሆነ የሃይማኖታችን ስያሜም ኦርቶዶክስ ተዋሕዶመባሉ በዚህ ምክንያት ነው ።

የት ተወለደ ?

በሚክያስ 5 ፥2 ። እንደተነገረው ጌታችን የተወለደው በቤተ ልሔም ከተማ በከብቶች በረት ውስጥ ነው ። ህዝቡ ሁሉ እን ዲጻፍ(እንዲቆጠር) ትእዛዝ ተላልፎ ስለነበረ ዮሴፍ እመቤታችንን ይዞ ሊመዘገብ ከናዝሬት ወደ ቤተ ልሔም በሄደበት ወቅት ከህዝቡ ብዛት የተነሳ ቤት አጥተው በከብቶች በረት ተጠግተው አደሩ በዚያም እያሉ የመውለጃዋ ወራት ደረሰና የዓለም መድኃኒት የሆነ ክርስቶስን በድንግልና ወለደች ። ማቴ 1 ፥ 18 ። ሉቃ 2 ፥ 1 ። በተወለደ ጊዜ አስቀድሞ ትንቢት ተነግሮላቸው የነበሩ ሰብአ ሰገል ፤ እስከ ቤተ ልሔም ድረስ ኮከብ እየመራቸው መጥተው ወድቀው ሰገዱለት ፤ ዕጅ መንሻውንም (ወርቅ ዕጣን ከርቤ) ሰጡት ። ማቴ 2 ፥ 11 ።

በአካባቢው የነበሩ እረኞችም በዙሪያው የሚያበራውን ብርሃን አይተው መልአኩ እየመራቸው ጌታ ከተወለደበት ዋሻ ደር ሰው የጌታን መወለድ አይተዋል ። ከመላእክት ጋር ሆነው

ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ወሰላም በምድር፤ በሰማያት ምስጋና ተደረገ በምድርም ሰላም ሆነ ለሰው ልጅ በጎ ፈቃድ

በማለት ዘምረዋል ። ሉቃ 2 ፥ 14 ።